Blog Archive

Monday 20 February 2017




ፆም እኛን አንጂ እግዚአብሔርን አይለውጠውም!



ክርስቲያናዊ ፆም  መፀሃፍ ቅዱስ ምን ይላል?
ክርስቲያኖች እንዲጾሙ መፅሃፍ ቅዱስ ትእዛዝ አይሰጥም:: ነገር ግን መጸሃፍ ቅዱስ ጾምን ጥሩ: ትርፋማ እና ጠቃሚ እንደሆነ ይገልፅልናል:: በሃዋርያት ስራ መፅሃፍ ላይ እንደተፃፈው አማኞች ትልቅ ውሳኔ ከመወሰናቸው በፊት ይጾሙ ነበር (የሐዋርያት ሥራ 13:2; 14:23):: ብዙውን ግዜ ጾምና ፀሎት የተቆራኙ (የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታ)ናቸው (ሉቃስ 2:37; 5:33):: ብዙውን ግዜ የጾም ትኩረት ምግብን ከመቀነስ ጋር ይያያዛል ነገር ግን የመጾም ዋና አላማ መሆን ያለበት ከዚህ አለም ትዕይንት አይንን አንስቶ ትኩረትን ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ማድረግ ነው:: ጾም ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት ምን ያክል serious እንደሆነ የምንገልፅበት መንገድ ነው:: ጾም አዲስ ምልከታን እና በእግዚአብሔር ላይ ያለንን ጥገኝነት እንድናደስ የረዳናል::

እንዲሁም ጾም በመፅሃፍ ቅዱስ በአብዛኛው ከምግብ ጋር የተያያዘ ይመስላል ነገር ግን ብዙ አይነት የጾም መንገዶች አሉ:: ለምሳሌ ትኩረታችንን ወደ እግዚአብሔር ለማድረግ የትኛውም ለጊዜው የምንተወው ወይም ከማድረግ የምንታቀበው ነገር እንደ መጾም ሊቆጠር ይችላል (1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 7:1-6):: ጾም የሰዓት ገደብ ሊኖረው ይገባል በተለይ ከምግብ በምንጾም ግዜ:: ጾም ስጋችንን የምንቀጣበት ሳይሆን ትኩረታችንን ወደ እግዚአብሔር የምናዞርበት ውድ ግዜ ነው:: መፅሃፍ ቅዱሳዊ ጾም ጥቅሙ የሰውነት ክብደት ለመቀነስ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ጋር የጠለቀ ህብረት ለማድረግ ነው:: ማንም ሰው ሊጾም ይችላል ነገር ግን መጾም የማይችሉ አሉ ለምሳሌ ስኳር በሽተኞች... እንዲጾሙ አይገደዱም:: ማንም ስው የሆነን ነገር በጊዜያዊነት አሳልፎ ከእግዚአብሔር ጋር ለመቀራረብ በመስጠት መጾም ይችላል::

አይናችንን ከዚህች ዓለም ነገሮቿ ላይ ማንሳት መለማመድ ትኩረታችንን ወደ ክርስቶስ ለማዞር ስኬታማ መንገድ ነው:: ጾም እግዚአብሔርን እኛ የምንፈልገውን ነገር እንዲሰጠን የምናደርግበት መንገድ አይደለም:: መጾማችን እኛን እንጂ እግዚአብሔርን አይለውጠውም:: ጾም ከሌሎች ክርስቲያኖች ይልቅ መንፈሳዊ ሆነን የምንታይበት መንገድም አይደለም:: ጾም መጾም ያለበት ትህትና በተሞላበት እና በደስተኝነት(joyful) አኳኋን ነው:: መፅሃፍ ቅዱስ በማቴዎስ ወንጌል 6:16-18 ሲናገር "ስትጦሙም፥ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደ ጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። አንተ ግን ስትጦም፥ በስውር ላለው አባትህ እንጂ እንደ ጦመኛ ለሰዎች እንዳትታይ ራስህን ተቀባ ፊትህንም ታጠብ፤ በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ይከፍልሃል።" ይላል:: ጾማችን ልማድ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ጋር የመገናኘት ልምምድ የምናደርግበት ውድ ግዜ ይሁንልን:: እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይባርካቹ::አሜን::

No comments:

Post a Comment